አምላካችን ማን ነዉ?

Written on 10/01/2016
Mamusha Fenta


“እረሱ (ክርስቶስ) የማይታየዉ አምላክ አምሳል ነዉ፤ ከፍጥረትም ሁሉ በፊት በኩር ነዉ፤ ሁሉ ነገር በእርሱ ተፈጥሮአል፤ በሰማይና በምድር ያሉ፣ የሚታዩና የማይታዩ፣ ዙፋናት ቢሆኑ ወይም ኀይላት፣ ገዦች ቢሆኑ ወይም ባለሥልጣናት፣ ሁሉም ነገር በእርሱና ለእርሱ ተፈጥሮአል። እርሱ ከሁሉ በፊት ነዉ፤ ሁሉ ነገር በአንድ ላይ ተያይዞ የጸናዉ በእርሱ ነዉ። እርሱ አካሉ የሆነችዉ የቤተክርስቲያን ራስ ነዉ፤ በሁሉ ነገር የበላይነት ይኖረዉ ዘንድ እርሱ የመጀመሪያ፣ ከሙታን መካከልም በኩር ነዉ።” (ቆላስያስ 1፡15-18)

እግዚአብሔር “ሕዝቤን ልቀቅ” ባለ ጊዜ ፈርኦን የተናገረዉ ሁልጊዜ ተገዳዳሪዎቻችን በህሊናችን የሚያቃጭሉት ጥያቄ ነዉ። ፈርኦን “ቃሉን እሰማ ዘንድ እስራኤልንስ እለቅቅ ዘንድ እግዚአብሔር ማን ነዉ?” ነበር ያለዉ (ዘጸ 5፡2)። ዛሬም “አምላክህ/ሽ  ማን ነዉ?” ለሚለን ቆላ 1 አስደናቂ እዉነታ ነዉ። አምላካችን ክርስቶስ ፍጥረተ ዓለሙን ካለመኖር ወደ መኖር ያመጣ ብቻ ሳይሆን አሁንም ፍጥረት ሥርዐት ይዞ እንዲቀጥል ሁሉን በአንድ ላይ አያይዞ ያስቀጥለዋል፣ ያጸናዋል። ፍጥረት ምን እንደሚያክል፣ በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ግዙፍ ከዋክብትና ክምችቶቻቸውም ምን እንደሚመስሉ ለማሰብ ያስቸግራል። እነኝህን ሁሉ በእጆቹ ይዞ የሚያጸናቸዉ… አምላካችን ነው (ኢሳ 40፡27-31)። ክርስቶስ የሁሉ ፈጣሪና የበላይ ነዉ። የኛ ችግርና ተግዳሮትማ ለእርሱ እንዴት ቀላል ነዉ? ስለሆነም  አማኝ ነፍሱን 

“እረፊ፣ አትጨነቂ፣ አትታወኪ፣ ዝም ብለሽ በኃያሉ አምላክሽ ታመኚ” ይበል፡፡